እንደነገርኩሽ… የሚወዱትን ሰው - ቀጥሮ እንደመጠበቅ፣ የነፍሰ ጡርን ሞት - አይቶ እንደመሳቀቅ፣ ባልታሰበ ናዳ - ተመትቶ እንደመድቀቅ፣ ከተስፋ ጉልላት - ተገፍቶ እንደመውደቅ፣ ታምር በበዛባት - በዚህች ቧልተኛ ዓለም፣ ከዚህ የበለጠ - ምንም ህመም የለም፡፡ አውቶብሱ ያማል፣ ሚኒባሱ ያማል፣ ላዳ ታክሲው ያማል፣ የማይጎል የሰው ጎርፍ ደራሽ ማዕበሉ፣ የእንባ ቅጥልጥሉ፣ ምን ብዬ ልንገርሽ - ያማል ይሄ ሁሉ፡፡ እና እንደነገርኩሽ… የሚወዱትን ሰው ቀጥረው ካረፈደ፣ የሚያፈቅሩትን ሰው ቀጥረው ካረፈደ፣ ነገር ተበላሸ - ህመም ተወለደ፡፡ ጨጓራ በገነ፣ እሳት በእንፋሎት መልክ በእህታ ተነነ፡፡ የሚሆነው ሳይሆን የማይሆነው ሆነ፡፡ ሁሉም ተቀይሮ ተተካ በሲቃ፣ ምን ብዬ ልንገርሽ ይህም ያማል በቃ፡፡ ወጪ ተራማጁ፣ አስመሳይ ሰጋጁ፣ ፀሐዩ ዝናቡ፣ የለምን ምክንያት የለምን ሰበቡ፣ ተቆራጭ አበባ ሊቆረጥ ማበቡ፣ ውል የለሽ ደመና ተራራ መክበቡ፣ እልፍ አዕላፍ ኮከብ ጨረቃን ማጀቡ፣ ደግሞ ለእሷ ግጥም እናቷን ጨረቃ፣ ምን ብዬ ልንገርሽ ይህም ያማል በቃ፡፡ እና እንደነገርኩሽ… ጉንጭ የማትሞላ ኬክ 10 ብር የሸጠ፣ የካፌ አሳላፊ ወደ እኔ አፈጠጠ፡፡ ዘይት የነካውን መንታ እጁን አጣምሮ፣ ምን ልታዘዝ ይላል ቁልቁል አቀርቅሮ፡፡ ምን ልታዘዝ ይላል… እንዴት ቅጥሉ ሰው ቅጥሉን ሰው ያዛል፣ ማኪያቶ ልዘዝ…? ካፑቺኖ ልዘዝ…? ጥቁ ቡና ልዘዝ…? ለምን ሰው አላዝም… መታዘዝ መናዘዝ ርግማን የሆነው፣ ካፌውን ሲያሳልፍ፣ ራሱ ግን የሚያልፍ፡፡ ቁልቁል አቀርቅሮ፣ ሞቱን ባንገት ቀብሮ፣ ምን ልታዘዝ ይላል… አንድ ማኪያቶ - ካንድ እሷ ጋር ልበል… አንድ ካፑችኖ - ካንድ እሷ ጋር ልበል… ከጥቁር ቡና ጋር - እሷን ...
ያላለቀ ድርሰት Written by አንተነህ ይግዛው “ኧረ ይብቃህ ደጀኔ!... አራት ሰዓት ሞላኮ!...” አሉ እትየ ስንዱ፣ መጋረጃውን ገለጥ አድርገው ከወደ ጓዳ ብቅ እያሉ፡፡ “አንቺ ግን ለምን ሰላም አትሰጪኝም!?...” ደጀኔ አቀርቅሮ ከሚጽፍበት ቀና በማለት በንዴት ጦፎ እስክርቢቶውን ወረወረ፡፡ “ስንቴ ልንገርሽ አክስቴ!?… በውስጤ የታመቀውን የደራሲነት ስሜት መተንፈስ እንጂ፣ የኮሌጅ ትምህርት አጠናቆ መመረቅ አይደለም የህይወቴ ጥሪ!” እየተንቀጠቀጠ ተናገረ፡፡ “የዛሬውስ የተለየ ነው!... ገና በማለዳ ንትርክ ጀመራችሁ?” የእማማ በለጡ ድምጽ በስተቀኝ ያለውን የኮምፔርሳቶ ግድግዳ አልፎ ተሰማ፡፡ ከጉዳይ የጣፋቸው አልነበረም፡፡ “ተው እንጂ ደጀኔ… ደህና ሂደህ ሂደህ አንድ አመት ሲቀርህ አትሰላች!” በትህትና መለሱለት፡፡ “አንቺኮ ችግርሽ ይሄ ነው!... የጀመርኩትን ትምህርት እንጂ፣ የጀመርኩትን ድርሰት ስለመጨረሴ አትጨነቂም!” ከተቀመጠበት ብድግ አለ፡፡ ሁለት አንቀጽ ጅምር አጭር ልቦለድ የጻፈባትን ወረቀት ከጠረጴዛው አንስቶ በፍጥነት ወደ ጓዳ አመራ፡፡ “እኔኮ ላንተ ብየ ነው!... ደሞም’ኮ አትጣፍ አላልኩህም፡፡ ከኮሌጅ ስትመለስ መጨረስ ትችላለህ” አሉት አክስቱ በትህትና ፈገግ ብለው፡፡ የአክስቱ ትህትና የገነፈለ ስሜቱን በረድ አደረገለት፡፡ እንደወትሮው አልተቆጡትም፡፡ እንደሌላው ጊዜ ልብ የሚሰብር ነገር አልተናገሩትም፡፡ “ደሞ አንተን ብሎ ደራሲ!... የአስር ሳንቲም ሻይ ቅጠል የማይገዛ እንቶፈንቶ መሞንጨሩን ትተህ፣ ትምህርትህን ብታጠና ይሻልሃል!” ብለው አልተሳለቁበትም፡፡ ወደ ጓዳ የጀመረውን ...